ምዕራፍ 17

ጥል ባለበት ዘንድ እርድ ከሞላበት ቤት በጸጥታ ደረቅ ቍራሽ ይሻላል።
2 አስተዋይ ባሪያ ነውረኛውን ልጅ ይገዛል፥ በወንድማማች መካከልም ርስትን ይካፈላል።
3 ማቅለጫ ለብር፥ ከውር ለወርቅ ነው፤ እግዚአብሔር ግን ልብን ይፈትናል።
4 ክፉ ሰው የበደለኛን ከንፈር ይሰማል፤ ሐሰተኛም ወደ ተንኰለኛ ምላስ ያደምጣል።
5 በድሀ የሚያላግጥ ፈጣሪውን ይሰድባል፤ በጥፋትም ደስ የሚለው ሳይቀጣ አይቀርም።
6 የሽማግሌዎች አክሊል የልጅ ልጆች ናቸው፤ የልጆችም ክብር አባቶቻቸው ናቸው።
7 ለሰነፍ የኵራት አነጋገር አይገባውም፤ ይልቁንም ሐሰተኛ ከንፈር ለመኰንን አይገባውም።
8 ገንዘብ ባደረገው ፊት መማለጃ እንደ ተዋበ ዕንቍ ነው፥ ወደ ዞረበትም ስፍራ ሁሉ ሥራውን ያቀናል።
9 ኃጢአትን የሚከድን ሰው ፍቅርን ይሻል፤ ነገርን የሚደጋግም ግን የተማመኑትን ወዳጆቹን ይለያያል።
10 መቶ ግርፋት በሰነፍ ጠልቆ ከሚገባ ይልቅ ተግሣጽ በአስተዋይ ሰው ጠልቆ ወደ ልቡ ይገባል።
11 ክፉ ሰው ዓመፃን ብቻ ይሻል፤ ስለዚህ ጨካኝ መልአክ ይላክበታል።
12 ሰነፍን በስንፍናው ከመገናኘት ልጆችዋ የተነጠቁባትን ድብ መገናኘት ይሻላል።
13 በመልካም ፋንታ ክፉን የሚመልስ፥ ክፉ ነገር ከቤቱ አትርቅም።
14 የጠብ መጀመሪያ እንደ ውኃ አፈሳሰስ ነው፤ ስለዚህ ጠብ ሳይበረታ አንተ ክርክርን ተው።
15 ኀጥኡን የሚያጸድቅና በጻድቁ ላይ የሚፈርድ፥ ሁለቱ በእግዚአብሔር ዘንድ አስጸያፊዎች ናቸው።
16 በሰነፍ እጅ የጥበብ መግዣ ገንዘብ መኖሩ ስለ ምንድር ነው? ጥበብን ይገዛ ዘንድ አእምሮ የለውምና።
17 ወዳጅ በዘመኑ ሁሉ ይወድዳል፤ ወንድምም ለመከራ ይወለዳል።
18 አእምሮ የጐደለው ሰው አጋና ይመታል፥ በባልንጀራውም ፊት ይዋሳል።
19 ዓመፃን የሚወድድ ክርክርን ይወድዳል፤ ደጁንም ዘለግ የሚያደርግ ውድቀትን ይሻል።
20 ጠማማ ልብ ያለው መልካምን አያገኝም፥ ምላሱንም የሚገለብጥ በክፉ ላይ ይወድቃል።
21 ሰነፍን የሚወልድ ኀዘን ይሆንበታል፥ የደንቆሮ ልጅም አባት ደስ አይለውም።
22 ደስ ያላት ልብ መልካም መድኃኒት ናት፤ ያዘነች ነፍስ ግን አጥንትን ታደርቃለች።
23 ኀጥእ የፍርድን መንገድ ለማጥመም ከብብት መማለጃን ይወስዳል።
24 በአስተዋይ ፊት ጥበብ ትኖራለች፤ የሰነፍ ዓይን ግን በምድር ዳርቻ ነው።
25 ሰነፍ ልጅ ለአባቱ ፀፀት ነው፥ ለወለደችውም ምሬት ነው።
26 ጻድቅን መቅጣት፥ ጨዋ ሰውንም በጻድቅነቱ መምታት መልካም አይደለም።
27 ጥቂት ቃልን የሚናገር አዋቂ ነው፥ መንፈሱም ቀዝቃዛ የሆነ አስተዋይ ነው።
28 ሰነፍ ዝም ቢል ጠቢብ ሆኖ ይቈጠራል፥ ከንፈሩንም የሚቈልፍ። ባለ አእምሮ ነው ይባላል።