ምዕራፍ 29

ብዙ ጊዜ ተዘልፎ አንገቱን ያደነደነ ድንገት ይሰበራል፥ ፈውስም የለውም።
2 ጻድቃን በበዙ ጊዜ ሕዝብ ደስ ይለዋል፤ ኀጥኣን በሠለጠኑ ጊዜ ግን ሕዝብ ያለቅሳል።
3 ጥበብን የወደደ ሰው አባቱን ደስ ያሰኛል፤ ጋለሞቶችን የሚከተል ግን ሀብቱን ያጠፋል።
4 ንጉሥ በፍርድ አገሩን ያጸናል፤ መማለጃ የሚወድድ ግን ያፈርሰዋል።
5 ወዳጁን በለዘበ ቃል የሚናገር ሰው ለእግሩ መርበብን ይዘረጋል።
6 በክፉ ሰው ዓመፃ ወጥመድ ይገኛል፤ ጻድቅ ግን ደስ ይለዋል፥ እልልም ይላል።
7 ጻድቅ የድሆችን ፍርድ ይመለከታል፤ ኀጥእ ግን እውቀትን አያስተውልም።
8 ፌዘኞች ከተማቸውን ያቃጥላሉ፤ ጠቢባን ግን ቍጣን ይመልሳሉ።
9 ጠቢብ ከሰነፍ ጋር ቢጣላ፥ ሰነፍ ወይም ይቈጣል ወይም ይስቃል፥ ዕረፍትም የለም።
10 ደምን ለማፍሰስ የሚሹ ሰዎች ፍጹሙን ሰው ይጠላሉ፥ ደግሞም የቅኑን ሰው ነፍስ ይሻሉ።
11 ሰነፍ ሰው ቍጣውን ሁሉ ያወጣል፤ ጠቢብ ግን በውስጡ ያስቀረዋል።
12 መኰንን ሐሰተኛ ነገርን ቢያደምጥ፥ ከእርሱ በታች ያሉት ሁሉ ዓመፅኞች ይሆናሉ።
13 ድሀና ግፈኛ ተገናኙ፤ እግዚአብሔር የሁለቱንም ዓይን ያበራል።
14 ለድሀ በእውነት የሚፈርድ ንጉሥ፥ ዙፋኑ ለዘላለም ይጸናል።
15 በትርና ተግሣጽ ጥበብን ይሰጣሉ፤ ያልተቀጣ ብላቴና ግን እናቱን ያሳፍራል።
16 ኀጥኣን ሲበዙ ኃጢአት ትበዛለች፤ ጻድቃን ግን ውደቀታቸውን ያያሉ።
17 ልጅህን ቅጣ ዕረፍትንም ይሰጥሃል፤ ለነፍስህም ተድላን ይሰጣታል።
18 ራእይ ባይኖር ሕዝብ መረን ይሆናል፤ ሕግን የሚጠብቅ ግን የተመሰገነ ነው።
19 ባሪያ በቃል አይገሠጽም፤ ቢያስተውል እንኳ አይመልስምና።
20 በቃሉ የሚቸኵለውን ሰው ብታይ፥ ከእርሱ ይልቅ ለሰነፍ ተስፋ አለው።
21 ባሪያውን ከሕፃንነቱ ጀምሮ በማቀማጠል የሚያሳድግ የኋላ ኋላ እንደ ጌታ ያደርገዋል።
22 ቍጡ ሰው ክርክርን ያነሣሣል። ወፈፍተኛ ሰውም ኃጢአትን ያበዛል።
23 ሰውን ትዕቢቱ ያዋርደዋል፤ መንፈሱን የሚያዋርድ ግን ክብርን ይቀበላል።
24 ከሌባ ጋር የሚካፈል ነፍሱን ይጠላል፤ መርገምን ይሰማል፥ ነገር ግን ምንም አይገልጥም።
25 ሰውን መፍራት ወጥመድ ያመጣል፤ በእግዚአብሔር የሚታመን ግን እርሱ ይጠበቃል።
26 ብዙ ሰዎች የሹምን ፊት ይሻሉ፤ የሰው ፍርድ ግን ከእግዚአብሔር ዘንድ ነው።
27 ኃጢአተኛ በጻድቃን ዘንድ አስጸያፊ ነው፤ በቀና መንገድ የሚሄደውም በኀጥኣን ዘንድ አስጸያፊ ነው።