ምዕራፍ 3

በይሁዳም ንጉሥ በኢዮሣፍጥ በአሥራ ስምንተኛው ዓመት የአክዓብ ልጅ ኢዮራም በእስራኤል ላይ በሰማርያ መንገሥ ጀመረ፥ አሥራ ሁለትም ዓመት ነገሠ።
2 ፤ በእግዚአብሔርም ፊት ክፉ አደረገ፤ ነገር ግን አባቱ ያሠራውን የበኣልን ሐውልት አርቆአልና እንደ አባቱና እንደ እናቱ አልነበረም።
3 ፤ ነገር ግን እስራኤልን ባሳታቸው በናባጥ ልጅ በኢዮርብዓም ኃጢአት ተያዘ፤ ከእርሱም አልራቀም።
4 ፤ የሞዓብም ንጉሥ ሞሳ ባለ በጎች ነበረ፤ ለእስራኤልም ንጉሥ የመቶ ሺህ ጠቦትና የመቶ ሺህ አውራ በጎች ጠጕር ይገብርለት ነበር።
5 ፤ አክዓብም ከሞተ በኋላ የሞዓብ ንጉሥ በእስራኤል ንጉሥ ላይ ዐመፀ።
6 ፤ በዚያም ጊዜ ንጉሡ ኢዮራም ከሰማርያ ወጥቶ እስራኤልን ሁሉ አሰለፈ።
7 ፤ ወደ ይሁዳም ንጉሥ ወደ ኢዮሣፍጥ። የሞዓብ ንጉሥ ዐምፆብኛልና ከእኔ ጋር በሞዓብ ላይ ለሰልፍ ትሄዳለህን? ብሎ ላከ። እርሱም። እወጣለሁ፤ እኔ እንደ አንተ፥ ሕዝቤም እንደ ሕዝብህ፥ ፈረሶቼም እንደ ፈረሶችህ ናቸው አለ።
8 ፤ ደግሞም። በምን መንገድ እንሄዳለን? አለ፤ እርሱም። በኤዶምያስ ምድረ በዳ መንገድ ብሎ መለሰ።
9 ፤ የእስራኤል ንጉሥና የይሁዳ ንጉሥ የኤዶምያስም ንጉሥ ሄዱ፤ የሰባትም ቀን መንገድ ዞሩ፤ ለሠራዊቱና ለተከተሉአቸውም እንስሶች ውኃ አልተገኘም።
10 ፤ የእስራኤልም ንጉሥ። ወዮ! እግዚአብሔር በሞዓብ እጅ አሳልፎ ይሰጣቸው ዘንድ እነዚህን ሦስቱን ነገሥታት ጠርቶአልና ወዮ አለ።
11 ፤ ኢዮሣፍጥም። በእርሱ እግዚአብሔርን የምንጠይቅበት የእግዚአብሔር ነቢይ በዚህ አይገኝምን? አለ። ከእስራኤልም ንጉሥ ባሪያዎች አንዱ። በኤልያስ እጅ ላይ ውኃ ያፈስስ የነበረው የሣፋጥ ልጅ ኤልሳዕ እዚህ አለ ብሎ መለሰ።
12 ፤ ኢዮሣፍጥም። የእግዚአብሔር ቃል በእርሱ ዘንድ ይገኛል አለ። የእስራኤል ንጉሥና ኢዮሣፍጥ የኤዶምያስም ንጉሥ ወደ እርሱ ወረዱ።
13 ፤ ኤልሳዕም የእስራኤልን ንጉሥ። እኔ ከአንተ ጋር ምን አለኝ? ወደ አባትህና ወደ እናትህ ነቢያት ሂድ አለው። የእስራኤልም ንጉሥ። አይደለም፥ በሞዓብ እጅ ይጥላቸው ዘንድ እግዚአብሔር እነዚህን ሦስት ነገሥታት ጠርቶአል አለው።
14 ፤ ኤልሳዕም። በፊቱ የቆምሁት የሠራዊት ጌታ ሕያው እግዚአብሔርን! የይሁዳን ንጉሥ ኢዮሣፍጥን ያላፈርሁ ብሆን ኖሮ አንተን ባልተመለከትሁና ባላየሁ ነበር።
15 ፤ አሁንም ባለ በገና አምጡልኝ አለ። ባለ በገናውም በደረደረ ጊዜ የእግዚአብሔር እጅ መጣችበት፤
16 ፤ እንዲህም አለ። እግዚአብሔር እንዲህ ይላል። በዚህ ሸለቆ ሁሉ ጕድጓድ ቆፈሩ።
17 ፤ እግዚአብሔርም እንዲህ ይላል። ነፋስ አታዩም፥ ዝናብም አታዩም፥ ይህ ሸለቆ ግን ውኃ ይሞላል፤ እናንተም ከብቶቻችሁም እንስሶቻችሁም ትጠጣላችሁ።
18 ፤ ይህም በእግዚአብሔር ዓይን ቀላል ነገር ነው፤ ደግሞም ሞዓባውያንን በእጃችሁ አሳልፎ ይሰጣል።
19 ፤ የተመሸጉትንና ያማሩትን ከተሞች ሁሉ ትመታላችሁ፥ የሚያፈሩትንም ዛፎች ሁሉ ትቈርጣላችሁ፥ የውኃውንም ምንጮች ሁሉ ትደፍናላችሁ፥ መልካሞችንም እርሻዎች ሁሉ በድንጋይ ታበላሻላችሁ።
20 ፤ በነጋውም የቍርባን ጊዜ ሲደርስ፥ እነሆ፥ ውኃ በኤዶምያስ መንገድ መጣ፥ ምድሪቱም ውኃ ሞላች።
21 ፤ ሞዓባውያንም ሁሉ ነገሥታት ሊወጉአቸው እንደ መጡ በሰሙ ጊዜ በወገባቸው ሰይፍ የሚታጠቁ ሁሉ ተሰበሰቡ፤ ወጥተውም በአገሩ ድንበር ላይ ቆሙ።
22 ፤ ማልደውም ተነሡ፤ ፀሐይም በውኃው ላይ አንጸባረቀ፥ ሞዓባውያንም በፊታቸው ውኃው እንደ ደም ቀልቶ አዩና። ይህ ደም ነው፤
23 ፤ በእርግጥ ነገሥታት እርስ በርሳቸው ተዋጉ፥ እርስ በርሳቸውም ተጋደሉ፤ ሞዓብ ሆይ፥ እንግዲህ ወደ ምርኮህ ሂድ አሉ።
24 ፤ ወደ እስራኤል ሰፈር በመጡ ጊዜ እስራኤላውያን ተነሥተው ሞዓባውያንን መቱ፥ እነርሱም ከፊታቸው ሸሹ፤ ሞዓባውያንንም እየመቱ ወደ አገሩ ውስጥ ገቡ።
25 ፤ ከተሞችንም አፈረሱ፤ በመልካሞቹም እርሻዎች ሁሉ ላይ እስኪሞሉ ድረስ እያንዳንዱ ሰው አንድ አንድ ድንጋይ ይጥል ነበር፤ የውኃውንም ምንጮች ሁሉ ደፈኑ፥ የሚያፈሩትንም ዛፎች ሁሉ ቈረጡ፤ የቂርሐራሴትን ድንጋዮች ብቻ አስቀሩ፤ ባለ ወንጭፎች ግን ከብበው መቱአት።
26 ፤ የሞዓብም ንጉሥ ሰልፍ እንደ በረታበት ባየ ጊዜ ሰይፍ የሚመዝዙ ሰባት መቶ ሰዎች ከእርሱ ጋር ወሰደ፥ ወደ ኤዶምያስም ንጉሥ ያልፉ ዘንድ ሞከሩ፤ አልቻሉምም።
27 ፤ በዚያም ጊዜ በእርሱ ፋንታ ንጉሥ የሚሆነውን የበኵር ልጁን ወስዶ ለሚቃጠል መሥዋዕት በቅጥሩ ላይ አቀረበው። በእስራኤልም ዘንድ ታላቅ ቍጣ ሆነ፤ ከዚያም ርቀው ወደ ምድራቸው ተመለሱ።