ምዕራፍ 9

ነቢዩም ኤልሳዕ ከነቢያት ልጆች አንዱን ጠርቶ እንዲህ አለው። ወገብህን ታጥቀህ ይህን የዘይት ማሰሮ በእጅህ ያዝ፥ ወደ ሬማት ዘገለዓድም ሂድ።
2 ፤ በዚያም በደረስህ ጊዜ የናሜሲን ልጅ የኢዮሣፍጥን ልጅ ኢዩን ታገኘዋለህ፤ ገብተህም ከወንድሞቹ መካከል አስነሣው፥ ወደ ጓዳም አግባው።
3 ፤ የዘይቱንም ማሰሮ ይዘህ በራሱ ላይ አፍስሰውና። እግዚአብሔር እንዲህ ይላል። በእስራኤል ላይ ንጉሥ ትሆን ዘንድ ቀባሁህ በለው፤ በሩንም ከፍተህ ሽሽ፥ አትዘግይም።
4 ፤ እንዲሁም ጕልማሳው ነቢይ ወደ ሬማት ዘገለዓድ ሄደ።
5 ፤ በገባም ጊዜ፥ እነሆ፥ የሠራዊት አለቆች ተቀምጠው ነበር፤ እርሱም። አለቃ ሆይ፥ ከአንተ ጋር ነገር አለኝ አለ። ኢዩም። ከማንኛችን ጋር ነው? አለ። እርሱም። አለቃ ሆይ፥ ከአንተ ጋር ነው አለ።
6 ፤ ተነሥቶም ወደ ቤቱ ገባ፤ ዘይቱንም በራሱ ላይ አፍስሶ እንዲህ አለው። የእስራኤል አምላክ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል። በእግዚአብሔር ሕዝብ በእስራኤል ላይ ንጉሥ ትሆን ዘንድ ቀባሁህ።
7 ፤ የባሪያዎቼን የነቢያትን ደም፥ የእግዚአብሔርንም ባሪያዎች ሁሉ ደም ከኤልዛቤል እጅ እበቀል ዘንድ የጌታህን የአክዓብን ቤት ትመታለህ።
8 ፤ የአክዓብም ቤት ሁሉ ይጠፋል፤ በእስራኤልም ዘንድ የታሰረውንና የተለቀቀውን ወንድ ሁሉ ከአክዓብ አጠፋለሁ።
9 ፤ የአክዓብንም ቤት እንደ ናባጥ ልጅ እንደ ኢዮርብዓም ቤት፥ እንደ አኪያም ልጅ እንደ ባኦስ ቤት አደርገዋለሁ።
10 ፤ ኤልዛቤልንም በኢይዝራኤል እርሻ ውሾች ይበሉአታል፥ የሚቀብራትም አታገኝም። በሩንም ከፍቶ ሸሸ።
11 ፤ ኢዩም ወደ ጌታው ባሪያዎች ወጣ፤ እነርሱም። ደኅና ነውን? ይህ እብድ ለምን መጣብህ? አሉት። እርሱም። ሰውዮውንና ነገሩን ታውቃላችሁ አላቸው።
12 ፤ እነርሱም። ሐሰት ነው፤ ንገረን አሉት፤ እርሱም። እግዚአብሔር እንዲህ ይላል። በእስራኤል ላይ ንጉሥ ትሆን ዘንድ ቀባሁህ ብሎ እንዲህ እንዲህ ነገረኝ አላቸው።
13 ፤ ሁሉም ፈጥነው ልብሳቸውን ወሰዱ፥ በሰገነቱ መሰላል እርከን ላይ ከእግሩ በታች አነጠፉት፥ ቀንደ መለከትም እየነፉ፥ ኢዩ ነግሦአል አሉ።
14 ፤ እንዲሁም የናሜሲ ልጅ የኢዮሣፍጥ ልጅ ኢዩ በኢዮራም ላይ ተማማለ። ኢዮራምና የእስራኤል ልጆች ሁሉ ከሶርያ ንጉሥ ከአዛሄል የተነሣ ሬማት ዘገለዓድን ይጠብቁ ነበር።
15 ፤ ንጉሡ ኢዮራም ግን ከሶርያ ንጉሥ ከአዛሄል ጋር በተዋጋ ጊዜ ሶርያውያን ያቈሰሉትን ቍስል ይታከም ዘንድ ወደ ኢይዝራኤል ተመልሶ ነበር። ኢዩም። ልባችሁስ ከእኔ ጋር ከሆነ በኢይዝራኤል እንዳያወራ ማንም ከከተማ ኰብልሎ አይውጣ አለ።
16 ፤ ኢዮራምም በዚያ ታምሞ ተኝቶ ነበርና ኢዩ በሰረገላው ላይ ተቀምጦ ወደ ኢይዝራኤል ሄደ። የይሁዳም ንጉሥ አካዝያስ ኢዮራምን ለማየት ወርዶ ነበር።
17 ፤ በኢይዝራኤልም ግንብ ላይ የቆመው ሰላይ የኢዩ ጭፍራ ሲመታ አይቶ። ጭፍራ አያለሁ አለ። ኢዮራምም። የሚገናኘው ፈረሰኛ ላክ፥ እርሱም። ሰላም ነውን? ይበለው አለ።
18 ፤ ፈረሰኛውም ሊገናኘው ሄዶ። ንጉሡ እንዲህ ይላል። ሰላም ነውን? አለ። ኢዩም። አንተ ከሰላም ጋር ምን አለህ? ወደ ኋላዬ አልፈህ ተከተለኝ አለ። ሰላዩም። መልእክተኛው ደረሰባቸው፥ ነገር ግን አልተመለሰም ብሎ ነገረው።
19 ፤ ሁለተኛም ፈረሰኛ ሰደደ፥ ወደ እነርሱም ደርሶ። ንጉሡ እንዲህ ይላል። ሰላም ነውን?አለ። ኢዩም። አንተ ከሰላም ጋር ምን አለህ? ወደ ኋላዬ አልፈህ ተከተለኝ አለ።
20 ፤ ሰላዩም። ደረሰባቸው፥ ነገር ግን አልተመለሰም፤ በችኰላ ይሄዳልና አካሄዱ እንደ ናሜሲ ልጅ እንደ ኢዩ አካሄድ ነው ብሎ ነገረው።
21 ፤ ኢዮራምም። ሰረገላ አዘጋጁ አለ፤ ሰረገላውንም አዘጋጁለት። የእስራኤልም ንጉሥ ኢዮራም የይሁዳም ንጉሥ አካዝያስ በሰረገሎቻቸው ተቀምጠው ወጡ፥ ኢዩንም ሊገናኙት ሄዱ፤ በኢይዝራኤላዊው በናቡቴ እርሻ ውስጥ አገኙት።
22 ፤ ኢዮራምም ኢዩን ባየ ጊዜ። ኢዩ ሆይ፥ ሰላም ነውን? አለ። እርሱም። የእናትህ የኤልዛቤል ግልሙትናዋና መተትዋ ሲበዛ ምን ሰላም አለ? ብሎ መለሰ።
23 ፤ ኢዮራምም መልሶ ነዳና ሸሸ፥ አካዝያስንም። አካዝያስ ሆይ፥ ዓመፅ ነው አለው።
24 ፤ ኢዩም በእጁ ቀስቱን ለጠጠ፥ ኢዮራምንም በጫንቃው መካከል ወጋው፤ ፍላጻውም በልቡ አለፈ፥ ወደ ሰረገላውም ውስጥ ወደቀ።
25 ፤ ኢዩም አለቃውን ቢድቃርን እንዲህ አለው። አንሥተህ በኢይዝራኤላዊው በናቡቴ እርሻ ጣለው፥ አንተና እኔ ጎን ለጎን በፈረስ ተቀምጠን አባቱን አክዓብን በተከተልን ጊዜ እግዚአብሔር እንዲህ ብሎ ይህን መከራ እንደ ተናገረበት አስብ።
26 ፤ በእውነት የናቡቴንና የልጆቹን ደም ትናንትና አይቻለሁ፥ ይላል እግዚአብሔር፥ በዚህም እርሻ እመልስብሃለሁ፥ ይላል እግዚአብሔር። ስለዚህ እግዚአብሔር እንደ ተናገረው ቃል ወስደህ በእርሻው ውስጥ ጣለው።
27 ፤ የይሁዳ ንጉሥ አካዝያስ ያንን ባየ ጊዜ በአትክልት ቤት መንገድ ሸሸ። ኢዩም። ይህን ደግሞ በሰረገላው ላይ ውጉት እያለ ተከተለው፤ በይብለዓምም አቅራቢያ ባለችው በጉር ዐቀበት ላይ ወጉት። ወደ መጊዶም ሸሸ፥ በዚያም ሞተ።
28 ፤ ባሪያዎቹም በሰረገላው ጭነው ወደ ኢየሩሳሌም ወሰዱት፥ በዳዊትም ከተማ በመቃብሩ ከአባቶቹ ጋር ቀበሩት።
29 ፤ በአክዓብም ልጅ በኢዮራም በአሥራ አንደኛው ዓመት አካዝያስ በይሁዳ ላይ ነገሠ።
30 ፤ ኢዩም ወደ ኢይዝራኤል መጣ፤ ኤልዛቤልም በሰማች ጊዜ ዓይንዋን ተኳለች፥ ራስዋንም አስጌጠች፥ በመስኮትም ዘልቃ ትመለከት ነበር።
31 ፤ ኢዩም በበሩ ሲገባ። ጌታውን የገደለ ዘምሪ ሆይ፥ ሰላም ነውን? አለችው።
32 ፤ ፊቱንም ወደ መስኮቱ አንሥቶ። ከእኔ ጋር ማን ነው? አለ። ሁለት ሦስትም ጃንደረቦች ወደ እርሱ ተመለከቱ።
33 ፤ እርሱም። ወደ ታች ወርውሩአት አለ፤ ወረወሩአትም፥ ደምዋም በግንቡና በፈረሶቹ ላይ ተረጨ፥ ረገጡአትም።
34 ፤ በገባም ጊዜ በላ ጠጣም፤ ከዚያም በኋላ። ይህችን የተረገመች እዩ፤ የንጉሥ ልጅ ናትና ቅበሩአት አለ።
35 ፤ ሊቀብሩአትም በሄዱ ጊዜ ከአናትዋና ከእግርዋ ከመዳፍም በቀር ምንም አላገኙም።
36 ፤ ተመልሰውም ነገሩት፤ እርሱም። በባሪያው በቴስብያዊ ኤልያስ። በኢይዝራኤል እርሻ የኤልዛቤልን ሥጋ ውሾች ይበላሉ፤
37 ፤ የኤልዛቤልም ሬሳ በኢይዝራኤል እርሻ መሬት ላይ እንደ ፍግ ይሆናልና ማንም። ይህች ኤልዛቤል ናት ይል ዘንድ አይችልም ብሎ የተናገረው የእግዚአብሔር ቃል ይህ ነው አለ።