ምዕራፍ 12

በዚያም ቀን። አቤቱ፥ ተቈጥተኸኛልና፥ ቍጣህንም ከእኔ መልሰሃልና፥ አጽናንተኸኛልምና አመሰግንሃለሁ።
2 ፤ እነሆ፥ አምላክ መድኃኒቴ ነው፤ ጌታ እግዚአብሔር ኃይሌና ዝማሬዬ ነውና፥ መድኃኒቴም ሆኖአልና በእርሱ ታምኜ አልፈራም ትላለህ።
3 ፤ ውኃውንም ከመድኃኒት ምንጮች በደስታ ትቀዳላችሁ።
4 ፤ በዚያም ቀን እንዲህ ትላላችሁ። እግዚአብሔርን አመስግኑ፥ ስሙንም ጥሩ፤ በአሕዛብ መካከል ሥራውን አስታውቁ፤ ስሙ ከፍ ያለ እንደ ሆነ ተናገሩ።
5 ፤ ታላቅ ሥራ ሠርቶአልና ለእግዚአብሔር ተቀኙ፤ ይህንም በምድር ሁሉ ላይ አስታውቁ።
6 ፤ አንቺ በጽዮን የምትኖሪ ሆይ፥ የእስራኤል ቅዱስ በመካከልሽ ከፍ ከፍ ብሎአልና ደስ ይበልሽ እልልም በዪ።