መጽሐፈ ኢዮብ።
ምዕራፍ 32
ኢዮብም ራሱን ጻድቅ አድርጎ ነበርና እነዚያ ሦስቱ ሰዎች መመለስን ተዉ።
2 ፤ ከራም ወገን የሆነ የቡዛዊው የባርክኤል ልጅ የኤሊሁ ቍጣ ነደደ፤ ከእግዚአብሔር ይልቅ ራሱን ጻድቅ አድርጎ ነበርና ኢዮብን ተቈጣው።
3 ፤ ደግሞም በኢዮብ ፈረዱበት እንጂ የሚገባ መልስ ስላላገኙ በሦስቱ ባልንጀሮቹ ላይ ተቈጣ።
4 ፤ ኤሊሁ ግን ከእርሱ ይልቅ ሽማግሌዎች ነበሩና ከኢዮብ ጋር መናገርን ጠብቆ ነበር።
5 ፤ ኤሊሁም በነዚህ በሦስቱ ሰዎች አፍ መልስ እንደሌለ ባየ ጊዜ ቍጣው ነደደ።
6 ፤ የቡዛዊውም የባርክኤል ልጅ ኤሊሁ ተናገረ እንዲህም አለ።  እኔ በዕድሜ ታናሽ ነኝ፥ እናንተ ግን ሽማግሌዎች ናችሁ፤  ስለዚህም ሰጋሁ፤ እውቀቴን እገልጥላችሁ ዘንድ ፈራሁ።
7 ፤ እንደዚህም አልሁ። ዓመታት በተናገሩ ነበር፥  የዓመታትም ብዛት ጥበብን ባስተማረች ነበር።
8 ፤ ነገር ግን በሰው ውስጥ መንፈስ አለ፥  ሁሉንም የሚችል የአምላክ እስትንፋስ ማስተዋልን ይሰጣል።
9 ፤ በዕድሜ ያረጁ ጠቢባን አይደሉም፥  ሽማግሌዎችም ፍርድን አያስተውሉም።  
10 ፤ ስለዚህም። ስሙኝ፤  እኔ ደግሞ እውቀቴን እገልጥላችኋለሁ አልሁ።  
11 ፤ እነሆ፥ ቃላችሁን በትዕግሥት ጠበቅሁ፤  የምትናገሩትን ነገር እስክትመረምሩ ድረስ፤  ብልሃታችሁን አዳመጥሁ።  
12 ፤ እንዲሁም ልብ አደረግሁ፤  እነሆም፥ በእናንተ መካከል ኢዮብን ያስረዳ፥  ወይም ለቃሉ የመለሰ የለም።  
13 ፤ እናንተም። ጥበብን አግኝተናል፤  እግዚአብሔር ነው እንጂ ሰው አያሸንፈውም እንዳትሉ ተጠንቀቁ።  
14 ፤ እርሱ ግን ቃሉን በእኔ ላይ አልተናገረም፤  እኔም በንግግራችሁ አልመልስለትም።  
15 ፤ እነርሱ ደነገጡ፥ ዳግመኛም አልመለሱም፤  የሚናገሩትንም አጡ።  
16 ፤ እነርሱ አልተናገሩምና፥  ቆመው ዳግመኛ አልመለሱምና እኔ በትዕግሥት እጠብቃለሁን?  
17 ፤ እኔ ደግሞ ፈንታዬን እመልሳለሁ፥  እውቀቴንም እገልጣለሁ፤  
18 ፤ እኔ ቃል ተሞልቻለሁና፥  በውስጤም ያለ መንፈስ አስገድዶኛልና።  
19 ፤ በተሐ ጠጅ እንደ ተሞላና ሊቀደድ እንደ ቀረበ አቁማዳ፥  ሊፈነዳ እንደማይችል እንደ ወይን ጠጅ  አቁማዳ፥ እነሆ፥ አንጀቴ ሆነ።  
20 ፤ ጥቂት እንድተነፍስ እናገራለሁ፤  ከንፈሬን ገልጬ እመልሳለሁ።  
21 ፤ ለሰው ፊት ግን አላደላም፤  ሰውንም አላቈላምጥም።  
22 ፤ በማቈላመጥ እናገር ዘንድ አላውቅምና፤  ያለዚያስ ፈጣሪዬ ፈጥኖ ከሕይወቴ ይለየኝ ነበር።