ምዕራፍ 116

ሃሌ ሉያ።

እግዚአብሔር የልመናዬን ድምፅ ሰምቶአልና ወደድሁት።
2 ጆሮውን ወደ እኔ አዘንብሎአልና በዘመኔ ሁሉ እጠራዋለሁ።
3 የሞት ጣር ያዘኝ፥ የሲኦልም ሕማም አገኘኝ፤ ጭንቀትንና መከራን አገኘሁ።
4 የእግዚአብሔርንም ስም ጠራሁ። አቤቱ፥ ነፍሴን አድናት።
5 እግዚአብሔር መሓሪና ጻድቅ ነው፥ አምላካችንም ይቅር ባይ ነው።
6 እግዚአብሔር ሕፃናትን ይጠብቃል፤ ተቸገርሁ እርሱም አዳነኝ።
7 ነፍሴ ሆይ፥ ወደ ዕረፍትሽ ተመለሺ፥ እግዚአብሔር መልካም አድርጎልሻልና፤
8 ነፍሴን ከሞት፥ ዓይኔንም ከእንባ፥ እግሬንም ከመሰናከል አድኖአልና።
9 በሕያዋን አገር በእግዚአብሔር ፊት እሄዳለሁ።
10 አመንሁ ስለዚህም ተናገርሁ፤ እኔም እጅግ ተቸገርሁ።
11 እኔም ከድንጋጤዬ የተነሣ። ሰው ሁሉ ሐሰተኛ ነው አልሁ።
12 ስላደረገልኝ ሁሉ ለእግዚአብሔር ምንን እመልሳለሁ?
13 የመድኃኒትን ጽዋ እቀበላለሁ፥ የእግዚአብሔርንም ስም እጠራለሁ።
14 በሕዝቡ ሁሉ ፊት ስእለቴን ለእግዚአብሔር እፈጽማለሁ።
15 የቅዱሳኑ ሞት በእግዚአብሔር ፊት የከበረ ነው።
16 አቤቱ፥ እኔ ባሪያህ ነኝ፥ ባሪያህ ነኝ፥ የሴት ባሪያህም ልጅ ነኝ፤ ሰንሰለቴን ሰበርህ።
17 ለአንተ የምስጋና መሥዋዕትን እሠዋለሁ፥ የእግዚአብሔርንም ስም እጠራለሁ።
18 በሕዝቡ ሁሉ ፊት ስእለቴን ለእግዚአብሔር እፈጽማለሁ፥
19 በእግዚአብሔር ቤት አደባባይ፥ ኢየሩሳሌም ሆይ፥ በመካከልሽም። ሃሌሉያ