ምዕራፍ 135

ሃሌ ሉያ። የእግዚአብሔርን ስም አመስግኑ፤ እናንተ የእግዚአብሔር ባሪያዎች ሆይ፥ አመስግኑት፥
2 በእግዚአብሔር ቤት ውስጥ፥ በአምላካችን ቤት አደባባይ የምትቆሙ።
3 እግዚአብሔር ቸር ነውና እግዚአብሔርን አመስግኑ፤ ለስሙ ዘምሩ፥ መልካም ነውና፤
4 እግዚአብሔር ያዕቆብን ለራሱ፥ እስራኤልንም ለመዝገቡ መርጦታልና፤
5 እግዚአብሔር ታላቅ እንደ ሆነ፥ ጌታችንም ከአማልክት ሁሉ እንዲበልጥ አውቄአለሁና።
6 በሰማይና በምድር በባሕርና በጥልቆች ሁሉ፥ እግዚአብሔር የወደደውን ሁሉ አደረገ።
7 ከምድር ዳር ደመናትን ያወጣል፤ በዝናብ ጊዜ መብረቅን አደረገ፤ ነፋሳትንም ከመዛግብቱ ያወጣል።
8 የግብጽን በኵር ልጆች ከሰው ጀምሮ እስከ እንስሳ ድረስ መታ።
9 ግብጽ ሆይ፥ በመካከልሽ በፈርዖንና በባሪያዎቹ ሁሉ ላይ ተኣምራትንና ድንቅን ሰደደ።
10 ብዙ አሕዛብን መታ፥ ብርቱዎችንም ነገሥታት ገደለ።
11 የአሞራውያንን ንጉሥ ሴዎንን፥ የባሳንንም ንጉሥ ዐግን፥ የከነዓንን መንግሥታት ሁሉ ገደለ፤
12 ምድራቸውንም ርስት አድርጎ ለእስራኤል ለሕዝቡ ርስት ሰጠ።
13 አቤቱ፥ ስምህ ለዘላለም ነው፥ ዝክርህም ለልጅ ልጅ ነው፤
14 እግዚአብሔር ለሕዝቡ ይፈርዳልና፥ ባሪያዎቹንም ይረዳልና።
15 የአሕዛብ ጣዖታት የብርና የወርቅ፥ የሰው እጅ ሥራ ናቸው።
16 አፍ አላቸው፥ አይናገሩምም፤ ዓይን አላቸው፥ አያዩምም፤
17 ጆሮ አላቸው፥ አይሰሙምም፤ እስትንፋስም በአፋቸው የለም።
18 የሚሠሩአቸው ሁሉ የሚታመኑባቸውም ሁሉ እንደ እነርሱ ይሁን።
19 የእስራኤል ቤት ሆይ፥ እግዚአብሔርን ባርኩት። የአሮን ቤት ሆይ፥ እግዚአብሔርን ባርኩት፤
20 የሌዊ ቤት ሆይ፥ እግዚአብሔርን ባርኩት እግዚአብሔርን የምትፈሩት ሆይ፥ እግዚአብሔርን ባርኩት።
21 በኢየሩሳሌም የሚያድር እግዚአብሔር ከጽዮን የተባረከ ነው። ሃሌ ሉያ።