ምዕራፍ 146

የሐጌና የዘካርያስ መዝሙር።

ሃሌ ሉያ። ነፍሴ ሆይ፥ እግዚአብሔርን አመስግኚ።
2 በሕይወቴ እግዚአብሔርን አመሰግናለሁ፤ በምኖርበት ዘመን ሁሉ ለአምላኬ እዘምራለሁ።
3 ማዳን በማይችሉ በሰው ልጆችና በአለቆች አትታመኑ።
4 ነፍሱ ትወጣለች ወደ መሬቱም ይመለሳል፤ ያን ጊዜ ምክሩ ሁሉ ይጠፋል።
5 የያዕቆብ አምላክ ረዳቱ የሆነ ተስፋውም በአምላኩ በእግዚአብሔር የሆነ ሰው ምስጉን ነው፤
6 እርሱም ሰማይንና ምድርን ባሕርንም፥ በእነርሱ ያለውንም ሁሉ የፈጠረ፤ እውነትን ለዘላለም የሚጠብቅ፤
7 ለተበደሉት የሚፈርድ፥ ለተራቡ ምግብን የሚሰጥ ነው። እግዚአብሔር የታሰሩትን ይፈታል፤
8 እግዚአብሔር የወደቁትን ያነሣል፤ እግዚአብሔር ዕውሮችን ጥበበኞች ያደርጋቸዋል፤ እግዚአብሔር ጻድቃንን ይወድዳል፤
9 እግዚአብሔር ስደተኞችን ይጠብቃል፤ ድሀ አደጎችንና ባልቴቶችን ይቀበላል፤ የኃጢአተኞችንም መንገድ ያጠፋል።
10 እግዚአብሔር ለዘላለም ይነግሣል፤ ጽዮን ሆይ፥ አምላክሽ ለልጅ ልጅ ነው። ሃሌ ሉያ።