ምዕራፍ 29

ከድንኳን በመውጣት ጊዜ፤ የዳዊት መዝሙር።

የአምላክ ልጆች ሆይ፥ ለእግዚአብሔር አምጡ። ክብርንና ምስጋናን ለእግዚአብሔር አምጡ።
2 የስሙን ክብር ለእግዚአብሔር አምጡ፥ በቅድስናው ስፍራ ለእግዚአብሔር ስገዱ።
3 የእግዚአብሔር ድምፅ በውኆች ላይ፥ የክብር አምላክ አንጐደጐደ፥ እግዚአብሔር በብዙ ውኆች ላይ።
4 የእግዚአብሔር ድምፅ በኃይል ነው፤ የእግዚአብሔር ድምፅ በታላቅ ክብር ነው።
5 የእግዚአብር ድምፅ ዝግባን ይሰብራል፤ እግዚአብሔር የሊባኖስን ዝግባ ይቀጠቅጣል።
6 እንደ ጥጃ ሊባኖስን፥ አንድ ቀን እንዳለው አውሬ ልጅ ስርዮንን ያዘልላቸዋል።
7 የእግዚአብሔር ድምፅ የእሳቱን ነበልባል ይቈርጣል።
8 የእግዚአብሔር ድምፅ ምድረ በዳውን ያናውጣል፥ እግዚአብሔር የቃዴስን ምድረ በዳ ያናውጣል።
9 የእግዚአብሔር ድምፅ ዋላዎችን ያጠነክራቸዋል፥ ጫካዎቹንም ይገልጣል፤ ሁሉም በመቅደሱ። ምስጋና ይላል።
10 እግዚአብሔር የጥፋት ውኃን ሰብስቦአል፤ እግዚአብሔር ለዘላለም ንጉሥ ሆኖ ይቀመጣል።
11 እግዚአብሔር ለሕዝቡ ኃይልን ይሰጣል፤ እግዚአብሔር ሕዝቡን በሰላም ይባርካል።