ምዕራፍ 30

ለቤቱ መመረቅ ምስጋና፤ የዳዊት መዝሙር።

አቤቱ፥ ተቀብለኸኛልና፥ ጠላቶቼንም ደስ አላሰኘህብኝምና ከፍ ከፍ አደርግሃለሁ።
2 አቤቱ አምላኬ፥ ወደ አንተ ጮኽሁ ምሕረትም አደረግህልኝ።
3 አቤቱ፥ ነፍሴን ከሲኦል አወጣሃት፥ ወደ ጕድጓድም እንዳልወርድ አዳንኸኝ።
4 ቅዱሳን ሆይ፥ ለእግዚአብሔር ዘምሩ፥ ለቅድስናውም መታሰቢያ አመስግኑ።
5 ቍጣው ለጥቂት ጊዜ ነው፥ ሞገሱ ግን ለሕይወት ዘመን፤ ልቅሶ ማታ ይመጣል፥ ጥዋት ግን ደስታ ይሆናል።
6 እኔም በደስታዬ። ለዘላለም አልታወክም አልሁ።
7 አቤቱ፥ በፈቃድህ ለሕይወቴ ኃይልን ሰጠሃት፤ ፊትህን መለስህ፥ እኔም ደነገጥሁ።
8 አቤቱ፥ ወደ አንተ ጠራሁ፥ ወደ አምላኬም ለመንሁ።
9 ወደ ጥፋት ብወርድ በደሜ ምን ጥቅም አለ? አፈር ያመሰግንሃልን? እውነትህንም ይናገራልን?
10 እግዚአብሔር ሰማ ማረኝም፤ እግዚአብሔር ረዳቴ ሆነኝ።
11 ክብሬ ትዘምርልህ ዘንድ ዝምም እንዳትል ልቅሶዬን ለደስታ ለወጥህልኝ፥ ማቄን ቀድደህ ደስታንም አስታጠቅኸኝ።
12 አቤቱ አምላኬ፥ ለዘላለም አመሰግንሃለሁ።