ምዕራፍ 144

ስለ ጎልያድ፤ የዳዊት መዝሙር።

እግዚአብሔር አምላኬ ይባረክ፥ ለእጆቼ ሰልፍን፥ ለጣቶቼም ዘመቻን የሚያስተምር፤
2 መሓሪዬና መሸሸጊያዬ፥ መጠጊያዬና መድኃኒቴ፤ ረዳቴና መታመኛዬም፤ ሕዝቤንም ከእኔ በታች የሚያስገዛልኝ።
3 አቤቱ፥ እርሱን ታውቀው ዘንድ ሰው ምንድር ነው? ታስብለት ዘንድ የሰው ልጅ ምንድር ነው?
4 ሰው ከንቱን ነገር ይመስላል፤ ዘመኑ እንደ ጥላ ያልፋል።
5 አቤቱ፥ ሰማዮችህን ዝቅ ዝቅ አድርጋቸው ውረድም፤ ተራሮችን ዳስሳቸው ይጢሱም።
6 መብረቆችህን ብልጭ አድርጋቸው በትናቸውም፤ ፍላጾችህን ላካቸው አስደንግጣቸውም።
7 -
8 እጅህን ከአርያም ላክ አድነኝም ከብዙ ውኆች፥ አፋቸውም ምናምንን ከሚናገር፥ ቀኛቸው የሐሰት ቀኝ ከሆነ፥ ከባዕድ ልጆች እጅ አስጥለኝ።
9 አቤቱ፥ አዲስ ቅኔ እቀኛልሃለሁ፤ አሥር አውታር ባለው በገና እዘምርልሃለሁ።
10 ለነገሥታት መድኃኒትን የሚሰጥ፥ ባሪያውን ዳዊትን ከክፉ ሰይፍ የሚያድነው እርሱ ነው።
11 አድነኝ፥ አፋቸውም ምናምንን ከሚናገር፥ ቀኛቸውም የሐሰት ቀኝ ከሆነ፥ ከባዕድ ልጆች እጅ አስጥለኝ።
12 ልጆቻቸው በጕልማስነታቸው እንደ አዲስ አትክልት የሆኑ፥ ሴቶች ልጆቻቸውም እንደ እልፍኝ ያማሩና ያጌጡ፤
13 ዕቃ ቤቶቻቸውም የተሞሉ በየዓይነቱ ዕቃ የሚሰጡ፥ በጎቻቸውም ብዙ የሚወልዱ፥ በማሰማርያቸውም የሚበዙ፥
14 ላሞቻቸውም የሚሰቡ፤ ቅጥራቸውም መፍረሻና መውጫ የሌለው፥ በአደባባዮቻቸውም ዋይታ የሌለ፤
15 እንደዚህ የሚሆን ሕዝብ የተመሰገነ ነው፤ እግዚአብሔር አምላኩ የሆነ ሕዝብ ምስጉን ነው።