ምዕራፍ 12

ለመዘምራን አለቃ፥ ስለ ስምንተኛ የዳዊት መዝሙር።

አቤቱ፥ አድነኝ፤ ደግ ሰው አልቆአልና፥ ከሰው ልጆችም መተማመን ጐድሎአልና።
2 እርስ በርሳቸው ከንቱ ነገርን ይናገራሉ፤ በሽንገላ ከንፈር ሁለት ልብ ሆነው ይናገራሉ።
3 የሽንገላን ከንፈሮች ሁሉ እግዚአብሔር ያጠፋቸዋል፥ ታላቅ ነገርን የምትናገረውን ምላስ፤
4 ምላሳችንን እናበረታለን፤ ከንፈራችን የእኛ ነው፥ ጌታችን ማን ነው? የሚሉትን።
5 ስለ ድሆች መከራ፥ ስለ ችግረኞች ጩኸት እግዚአብሔር። አሁን እነሣለሁ ይላል፤ መድኃኒትን አደርጋለሁ፥ በላዩም እገልጣለሁ።
6 በምድር ላይ እንደ ተፈተነ ሰባት ጊዜ እንደ ተጣራ ብር። የእግዚአብሔር ቃላት የነጹ ቃላት ናቸው።
7 አቤቱ፥ አንተ ጠብቀን፥ ከዚህችም ትውልድ ለዘላለም ታደገን።
8 በሰው ልጆች ዘንድ ምናምንቴ ከፍ ከፍ ባለ ጊዜ ክፉዎች በዙሪያው ሁሉ ይመላለሳሉ።