ምዕራፍ 38

ለሰንበት መታሰቢያ፤ የዳዊት መዝሙር።

አቤቱ፥ በቍጣህ አትቅሠፈኝ፥ በመዓትህም አትገሥጸኝ።
2 ፍላጾችህ ወግተውኛልና፥ እጅህንም አክብደህብኛልና።
3 ከቍጣህ የተነሣ ለሥጋዬ ጤና የለውም፤ ከኃጢአቴም የተነሣ ለአጥንቶቼ ሰላም የላቸውም።
4 ኃጢአቴ በራሴ ላይ ከፍ ከፍ ብሎአልና፥ እንደ ከባድ ሸክምም በላዬ ከብዶአልና።
5 ከስንፍናዬ የተነሣ ቍስሌ ሸተተ በሰበሰም፤
6 እጅግ ጐሰቈልሁ ተዋረድሁም፥ ሁልጊዜም በትካዜ እመላለሳለሁ።
7 ነፍሴ ስድብን ተሞልታለችና፥ ለሥጋዬም ጤና የላትምና።
8 ታመምሁ፤ እጅግም ተቸገርሁ፥ ከልቤ ውዝዋዜም የተነሣ ጮኽሁ።
9 አቤቱ፥ ፈቃዴ ሁሉ በፊትህ ነው፥ ጭንቀቴም ከአንተ አይሰወርም።
10 ልቤ ደነገጠብኝ፥ ኃይሌም ተወችኝ፥ የዓይኖቼም ብርሃን ፈዘዘ።
11 ወዳጆቼም ባልንጀሮቼም ከቍስሌ ገለል ብለው ቆሙ፥ ዘመዶቼም ርቀው ቆሙ።
12 ነፍሴንም የሚሹአት በረቱብኝ፥ መከራዬንም የሚፈልጉ ከንቱን ተናገሩ፥ ሁልጊዜም በሽንገላ ይመክራሉ።
13 እኔ ግን እንደማይሰማ ደንቆሮ አፉንም እንደማይከፍት ዲዳ ሆንሁ።
14 እንደማይሰማ ሰው በአፉም ተግሣጽ እንደሌለው ሰው ሆንሁ።
15 አቤቱ፥ በአንተ ታምኛለሁና፤ አቤቱ አምላኬ፥ አንተ ትሰማኛለህ።
16 ጠላቶቼ በእኔ ላይ ደስ እንዳይላቸው ብያለሁና፥ እግሮቼም ቢሰናከሉ ራሳቸውን በእኔ ላይ ከፍ ከፍ ያደርጋሉ።
17 እኔስ ወደ ማንከስ ቀርቤአለሁና፥ ቍስሌም ሁልጊዜም በፊቴ ነውና።
18 በደሌን እናገራለሁና፥ ስለ ኃጢአቴም እተክዛለሁ።
19 ጠላቶቼ ሕያዋን ናቸው ይበረቱብኝማል፥ በጠማማነትም የሚጠሉኝ በዙ።
20 ጽድቅን ስለ ተከተልሁ፥ በበጎ ፋንታ ክፉን የሚመልሱልኝ ይጠሉኛል።
21 አቤቱ፥ አንተ አትጣለኝ፤ አምላኬ፥ ከኔ አትራቅ።
22 አቤቱ መድኃኒቴ፥ እኔን ለመርዳት ፍጠን።